

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ክልል በመጪው ጥር ወር ለሚያካሄደው ህዝበ ውሳኔ በአንድ ዞንና በሁለት ልዩ ወረዳዎች ለሚገኙ ተፈናቃዮች የሚያገለግሉ የምርጫ ጣቢያዎችን መክፈቱን ተከትሎ “መንግሥት ከምርጫው ይልቅ መሠረታዊ የምግብ ድጋፍ በምናገኝበት ሁኔታ ላይ ትኩረት እንዲሰጥ እንፈልጋለን” ስሉ ተፈናቃይ የህዝበውሳኔ ተመዝጋቢዎች ጠይቋል።
በደቡብ ክልል አሁን ላይ በህዝበ ውሳኔ እልባት ያገኛል የተባለው የአደረጃጀት ጥያቄ በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች ለግጭት መንስኤ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በተለይ በደራሼ እና በአሌ ልዩ ወረዳዎች የመዋቅር ጥያቄ ባስነሳው ግጭት በመቶዎች ሲሞቱ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ቤት ንብረታቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ዶቼ ቬለ በተደጋጋሚ ሲዘግብ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ታዲያ እነኝህን ተፈናቃዮች በህዝበ ውሳኔው ለማሳተፍ ያስችለኛል ያለውን ተጨማሪ ሰባት የልዩ ምርጫ ጣቢያዎች መክፈቱን አስታውቋል፡፡
የልዩ ምርጫ ጣቢያዎቹ የተከፈቱት በኮንሶ ዞን እንዲሁም በደራሼ እና አሌ ልዩ ወረዳዎች ውስጥ ነው ፡፡ የልዩ ምርጫ ጣቢያዎቹ መቋቋም በተፈናቃይ መጠለያ ጣቢያዎቹ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች በህዝበ ውሳኔው እንዲሳተፉ ለማድረግ እንደሚያስችል ቦርዱ ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በመጠለያ ጣቢያዎች ለሚገኙ ተፈናቃዮች የከፈታቸው ሰባት ልዩ የምርጫ ጣቢያዎች ከባለፈው ቅዳሜ ጀምሮ መራጮችን እየመዘገቡ ይገኛሉ፡፡ ያም ሆኖ በኮንሶ ዞንና በደራሼ ልዩ ወረዳዎች የሚገኙ ተፈናቃዮች ግን በህዝበ ውሳኔው ዙሪያ አዎንታዊም አሉታዊም አስተያየቶችን እየሰነዘሩ ይገኛሉ፡፡ አንዳንዶች በዕድሉ ተጠቅመው የመራጭነት ካርድ መውሰዳቸውን ሲናገሩ በአንፃሩ ሌሎች ደግሞ ከምርጫው ይልቅ የምግብና የመጠለያ ጉዳይ ያሳሰባቸው መሆኑን ነው ለዶቼ ቬለ DW የገለጹት ፡፡
በተፈናቃዮች መጠለያ አካባቢ በተከፈለው የምርጫ ጣቢያ የመራጮች ምዝገባ ከአሌ ልዩ ወረዳ ተፋናቅለው በኮንሶ ዞን ቀርቀርቴ ቀበሌ ተጠልለው እንደሚገኙ የሚናገሩት ጋሻው ኦርካይዶ እርሳቸው ባለቤታቸውንና ሦስት የደርሱ ልጆቻቸው ባለፈው ቅዳሜ የመራጭነት ካርድ መውሰዳቸውን ይናገራሉ፡፡ አዲሱ ክልል ከተዋቀር አሁን ላይ የሚታዩ ችግሮች ሊሻሻሉ ይችላሉ የሚል እምነት እንዳላቸው የሚናገሩት የቀርቀርቴ ቀበሌ ነዋሪው ጋሻው ‹‹ በተለይ ከአጎራባች የደራሼ እና የአሌ ወረዳዎች ጋር የሚታየው ደም ያፈሰሰ ግጭት በአንድ አስተዳደር ሥር ከተመራ መፍትሄ ያገኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

የደራሼ ልዩ ወረዳ ተፈናቃይ የሆኑት ባደግ ማሞ ግን ከጋሻው በተቃራኒ ጥርጥሬና ተስፋ መቁረጥ ይስተዋልባቸዋል፡፡ ከልዩ ወረዳው ሀጤያ ቀበሌ ተሰደው በጊዶሌ ከተማ በዘመድ ቤት ተጠልለው እንደሚገኙ የሚናገሩት ባደግ ‹‹መንግሥት ከምርጫው ይልቅ መሠረታዊ የምግብ ድጋፍ በምናገኝበት ሁኔታ ላይ ትኩረት እንዲሰጥ እፈልጋለሁ፡፡ በተለይም የወደሙ ቤቶች ዳግም ተሠርተው ወደ ቀደመ መንደራችን ለመመለስ ተደጋጋሚ ጥያቄዎችን ብናቀርብም አሁንድረስ ሰሚ ጆሮ አላገኘንም፡፡ ወይ በቂ ድጋፍ አላገኘን አሊያም ወደ ቦታችን ተመልሰን አላረስን፡፡ አሁን ላይ በመንግሥት ላይ ያለን ተስፋ ተሟጧል ›› ብለዋል ስል ዶቼቬሌ ዘግቧል፡፡
ተፈናቃይ ባለበት የልዩ ምርጫ ጣቢያዎቹ መቋቋም በተፈናቃይ መጠለያ ጣቢያዎቹ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች በህዝበ ውሳኔው እንዲሳተፉ መደረጉ እውነትም ተፈናቃዮች እንዲመርጡ ሳይሆን ምናልባት የምርጫ ካርድ የሚወስድ ሰው ባለመኖሩ የምርጫ ውጤት ላይ ተፅዕኖ ለማሳደር ሆን ተብሎ የተደረገ ነው ሚል ብዙዎች ስጋት ገልጿል።