በዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርስቲ የ2014 1ኛ ሩብ ዓመት አፈጻጸም ሪፖርት እና በ2014 2ኛ ሩብ ዓመት ሊከናወኑ በሚገቡ ተግባራት ዕቅድ ላይ ያተኮረ ውይይት ከዩኒቨርሲቲው ካውንስል አባላት ጋር በዛሬው ዕለት ተካሂዷል፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ክቡር ፕሮፌሰር ታከለ ታደሰ ተቋሙ ሰላማዊ እንዲሆን እንደሚሰራና ዩኒቨርሲቲው እንዳይረጋጋ የሚያደርጉ ሰዎችን የማጋለጥ ሥራ እንደሚሰራ ጠቁመው በጥንካሬ የተቀመጡ ጉዳዮችን በማቀጠልና በድክመት የታዩትን በማረም መልካም አስተዳደር በዩኒቨርሲቲው እንዲሰፍን ይሰራል ብለዋል፡፡
ፕሬዝዳንቱ አክለውም የመምህራን ልማት ላይ ትኩረት በመስጠት በመስራት ወርክሾፖችን በማደራጀት፣ የላይብራሪና የላቦራቶሪ ግብዓቶችን በማሟላት በትምህርት ጥራት ላይ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡
በመቀጠልም ፕሮፌሰሩ በዩኒቨርሲቲው ብልሹ አሰራር በተለይም በገንዘብ የሚገለጥ ሙስና ብቻ ሳይሆን በቅጥር፣ በተማሪዎች ኩረጃ፣ በተማሪዎች ውጤት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋል ሙስናን ከወትሮው በተሻለና ሁሉአቀፍ በሆነ መልኩ መታገል የቅድሚያ ቅድሚያ ተሰጥቶት የሚሰራ መሆኑን አስቀምጠዋል።
በዩኒቨርሲቲው አካባቢያዊነትን በማስወገድ ተቋሙ ዓለም አቀፋዊና ሀገር አቀፋዊ እንደሆነ በማረጋገጥና ህብረ ብሔራዊነት በማስፈን መሥራት ከሁሉ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አባላት የሚጠበቅ መሆኑን ፕሮፌሰሩ ገልፀዋል፡፡
እንደ ዩንቨረስቲው ኮሙኒኬሽን ዳይርክቶሬት ዘገባ በመርሃ ግብሩ ላይ የዩኒቨርሲቲው የ2014 ዓ.ም 1ኛ ሩብ ዓመት አፈጻጸም ሪፖርት እና በቀጣዩ ሩብ ዓመት ሊከናወኑ የሚገቡ ተግባራት ዕቅድ በዩኒቨርሲቲው ፕላንና ፕሮግራም ዳይሬክተር ዶ/ር ደነቀ ዳና ቀርቦ ከካውንስል አባላት ጋር ውይይት ተካሂዷል፡፡
በዩኒቨርሲቲው በአዲስ መልክ የተሰራው ተቋማዊ ዌብ ሳይት አሰራር የተመለከተ ሪፖርት ቀርቦም ከተሳታፊዎች አስተያየት ተሰጥቶበታል፡፡