

የዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ በሰሜኑ ኢትዮጵያ ዩንቨርስቲዎች ፀጥታ ችግር ምክንያት ወደ ዩንቨርስቲው የተቀላቀሉ 270 ተማሪዎችን በዛሬው ዕለት አስመረቀ
በትግራይ ክልል በአክሱምና አድግራት ዩንቨረሲቲ ትምህርታቸውን ስከታተሉ የነበሩ በተፈጠረው ፀጥታ ችግር ምክንያት ወደ ዎላይታ ሶዶ ዩንቨርስቲ በከፍተኛ ትምህርት ተቋም ምደባ በማግኘት የተቀላቀሉ ተማሪዎች በዛሬው ዕለት በተለያዩ ትምህርት ዘርፍ ተመርቀዋል።
በሀገሪቱ ተከስቶ በነበረው የጸጥታ ስጋት በሰሜኑ ከሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መካከል ከአክሱም፣ አድግራት እና ወልዲያ ዩኒቨርሲቲዎች 726 ተማሪዎች በትምህርት ሚኒስቴር ተመድበው በዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ ቆይተዋል።

ምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሙላቱ ዴአ በሀገራችን ሰሜኑ ጦርነት ዩኒቨርሲቲዎች በመዘጋታቻቸዉ ምክንያት የወደፊት ተሰፋችዉ እንዳይጨልም የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ትምህርት ሚኒስቴር በጊዚያዊነት ዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የተመደቡ ተማሪዎች የሚጠበቅባቸውን ግዴታ በመወጣት ለመጀመሪያ ዙር ምረቃ በመብቃታቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።

ምሩቃን በትምህርት ላይ ቆይታችሁ ብዙ አስቸጋሪ ሁኔታዎችንና የሕይወት ምዕራፎችን አልፋችሁ ለዛሬዋ ቀን በመብቃታችሁ በእጅጉ ልትደሰቱና ልትኮሩ ይገባል ያሉት ዶ/ር ሙላቱ ዴአ፤ በዩኒቨርሲቲ ቆይታችሁ ያካበታችሁትን እውቀትና ክህሎትን ከትጋትንና ሙሉ መሰጠት ጋር ለቀጣይ የሥራ ዘመን ማንኛውንም ፈተና በጽናት በመሻገር ራሳችሁን አዘጋጁ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ የዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፕ/ር ታከለ ታደሰ መንግስት ለከፍተኛ ትምህርት በሰጠው ልዩ ትኩረት ከዚህ ቀደም የነበረው የጥራት፣ የተገቢነት፣ የተደራሽነት እና የፍትሃዊነት ችግር ተቀርፎ ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ከድህነትና ኃላቀርነት ተላቃ በኢኮኖሚ ራሷን ችላና ተወዳዳሪ ሆና እንድትቀጥል የሚያስችሉ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ቢኖሯትም እነዚህንም በብቃት ሊፈጽሙ የሚችሉ በዕውቀት፣ በክህሎትና በመልካም ስነ-ምግባር የታነጸና የተሟላ ስብዕና ያላቸው ፈጻሚዎች በለሉበት ልማት የማይታሰብ በመሆኑ መንግሥት ለከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል ፕሬዝዳንቱ።

ሃገርቱ እያስመዘገበች ላለችው ዘላቂ የልማት ሥራዎች ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው የሚወጡ ምሁራን የአንበሳውን ድርሻ የሚወስዱ መሆኑን ፕ/ር ታከለ ተናግረው፤ በተለይም ሃገሪቱ በለውጥ ጎዳና ባለችበት በዚህ ወቅት በሚትመረቁ በዛሬ ተመራቂዎች ላይ ታላቅ ሀገራዊ ኃላፊነት የተጣለባችሁ መሆኑንን አሳስበዋል።
ምሩቃን በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው እልህ አስጨራሽ ተጋድሎ በማድረግ ትምህርታቸውን በድል ማጠናቀቃቸው የድል ጅማሮ መሆኑን ፕሬዝዳንቱ ገልጸው፤ በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን ዕውቀትና ክህሎት ወደ ሥራ ዓለም ሲገቡ በተግባር ላይ በማዋል ሀገራቸውን ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁለንተናዊ ዕድገት በላቀ ሁኔታ በማስቀጠል መላውን ህበረሰቡን በቅንነትና በታማኝነት ለማገልገል ከወዲሁ ዝግጁ እንዲሆኑ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የትምህርት ጥራት ለማሻሻል ቤተ ሙከራዎች፣ ዲጂታል ቤተ መጽሐፍትንና ወርክሾፖችን የማደራጀት እንዲሁም የመምህራን ብቃት ለትምህርት ጥራት መረጋገጥ ከፍተኛ ሚና ያለው መሆኑ በማመን የመምህራን ልማት ላይ ከፍተኛ እርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ዩኒቨርሲቲው ለየአካባቢው ማህበረሰብን የመማር እና የመለወጥ ፍላጎት ከማርካቱ ባሻገር በምሁራን በሚከናወኑ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምሮች እንዲሁም የማህበረሰብ አገልግሎቶች ተግባራት ተደራሽ በመሆናቸው የማህበረሰቡ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ከፍተኛ ሚና ተወጥቷል ሲሉ ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።
ዩኒቨርሲቲው ከመንግስት የተሰጠውን ተልዕኮ ከግብ ለማድረስ በተለያዩ የትምህርት መርሃ ግብሮች ተማሪዎችን በማሰልጠን ለሀገሪቱ ልማት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝ ፕሬዝዳንቱ ተናግረው፤ በዛሬው እለትም ለ12ኛ ዙር ከተለያዩ ዩንቨርስቲዎች በፀጥታ ምክኒያት ወደ ዩንቨርስቲው የገቡ ተማሪዎችን በሚመረቁበት መድረክ በመገኘታቸው የተሰማቻውን ከፍተኛ ደስታ ገልጸዋል።
የትምህርት ልማት ሥራዎች ስኬት ቀጣይነት እንዲኖረው ለማድረግ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋሟት ተመርቀው የሚወጡ ምሁራን የአንበሳውን ድርሻ የሚወስዱ መሆናቸውን ፕ/ር ታከለ ታደሰ ገልጸው፤ ከአስቸጋሪ ሁኔታ አልፎ በአዲስ ምዕራፍ፥ በአዲስ ተስፋ በዛሬ ዕለት የሚመረቁ ምሩቃን ላይ ታላቅ ሀላፊናትና ሀደራ የተጣለባቸው መሆኑንም ጠቁመዋል።
ምሩቃን በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን እውቀትና ክዕሎት ወደ ሥራ አለም ሲገቡ በተግባር ላይ በማዋል ሃገሪቱ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች የጀመረችውን ሁለንተናዊ እድገት በላቀ ሁኔታ ለማስቀጠል በሚደረገው ከፍተኛ ርብርብ የድርሻቸውን ሚና እንዲወጡ ፕ/ር ታከለ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
