የጎፋ እና ኦይዳ ብሔረሰቦች ባህላዊ እሴቶችን የማስተዋወቅና የማልማት ተግባር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የጎፋ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ገልጿል።

የጎፋ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ከዞኑ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት መምሪያ ጋር በመተባበር የአፈፃፀም ሥራ አመራርና ሚዛናዊ ውጤት ተኮር ዕቅድ ዝግጅት ትግበራና ምዘና ዙሪያ ለተቋሙ ባለሙያዎች ስልጠና ሰጥቷል።

በስልጠናው የባህል ታሪክ ቅርስ ጥናት ልማት፣ የቋንቋ ሥነ-ጥበብ ጥናት እና ልማት፣ የቱሪስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ልማት እና ብቃት መረጋገጥ፣ የቱሪስት መስህቦ ጥናት እና ልማት ዋና ሥራ ሂደቶች፣ የሰው ሀብት ሥራ አመራር እና ደጋፊ ሥራ ሂደቶችና ፈፃሚ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል።

የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ ድንበሩ ድርቤ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት የመምሪያው ራዕይ እና ተልዕኮ ለማሳካት የዘርፉ ባለሙያዎች በዕቅድ በመመራት የተጣለባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ለማስቻል የተዘጋጀ ስልጠና መሆኑን ተናግረዋል።

አቶ ድንበሩ አክለውም መምሪያው የጎፋ እና ኦይዳ ብሔረሰቦች ባህል፣ ታሪክና ቋንቋ የማስተዋወቅና የማልማት ተግባር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የዞኑ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት መምሪያ የርፎርም ጉዳዮች ክትትል፣ ድጋፍ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ከተማ መርጊያ የተቋሙን ተልዕኮ በብቃት ለመወጣትና ከስትራቴጂ ዕቅድ ጋር በማስተሳሰር በፈፃሚ ደረጃ ያለውን የግንዛቤ እጥረት ችግር ለመቅረፍ ስልጠናው አጋዥ መሆኑን ተናግረዋል።

አቶ ከተማ አያይዘውም በ2015 ዓ.ም ስታንዳርድን የጠበቀ ዕቅድ በማዘጋጀትና በመተግበር ግንባር ቀደም ተሞክሮ የሚቀሰምበት ተቋም ለማድረግ ያለመ ስልጠና መሆኑን ገልጸዋል።

በስልጠናው ተሳታፊ የነበሩ ባለሙያዎች በበኩላቸው በዕቅድ አዘገጃጀትና አስፈላጊነት ዙርያ ቀደም ስል የነበራቸውን የግንዛቤ እጥረት እንደሚቀርፍላቸውና የተሻለ አፈፃፀም እንዲያስመዘግቡ ስልጠናው አቅም እንደሚፈጥርላቸው ተናግረዋል ስል የዞኑ ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

%d bloggers like this: