ለመዝረፍና ለማዘረፍ የተነቃበት ሌባ ሲባረር በምስጢር ያልተነቃ ሌባ እየመጣ ይሁን❓

የዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ሀገሪቱ ውስጥ ካሉት አብዛኛዎቹ ዩኒቨርሲቲዎች በከፋ ደረጃ ስሙ ከአሰተዳደራዊ ብቃት ጉድለት፤ ምዝበራና ሌብነት ጋር በተያያዘ ሲነሳ ቀይቶ ኋላ ብዙ መቶ ሚልየን የህዝብ ገንዘብ ከፋይናንስ ሥርዓት ውጭ መመዝበሩ በኦዲት ተጣሪቶ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ሥልጣን በተሰጠው ጉዳዩ በሚመለከተው ኮሚቴ በኩል ለህዝብ ይፋ መደረጉ ይታወቃል፡፡

በፋይናንስ ሪፖርት አማካይኝነት ገንዘብን የተመለከተ ብክነትና ምዝበራው ለህዝብ የተገለፀ ቢሆንም ማነጅመንቱ በተቋሙና በሀገር ላይ ያደረሰው ጉዳት ግን በገንዘብ ምዝበራ ከሚተመነው በላይ እጅግ የላቀ ነው፡፡

ተቋሙ በአደረጃጀት አንጻር ሀገሪቱ ውስጥ ካሉት በተለምዶ ሶስተኛ ትውልድ ( 3rd generation ) ዩኒቨርሲቲዎች ከሚባሉት ምድብ ቢሆንም በተቋማዊ ቁመናው ግን ከአነዚህ ያነሰና አራተኛ ትውልድ ተርታ የሚመደብ እንዲሆን አድርገውታል፡፡

የአሰራር ብልሹነት በዚህኛው ማነጅመንት ብሶ ይገኝ እንጂ ዩኒቨርሲቲው ከተመሰረተ አንስቶ የዩኒቨርሲቲው የበላይ አመራር በብቃቸው ሳሆን በፖለቲከኞች ቡራኬና ግለሰቦቹ ለካድሬዎች በሚኖራቸው ቅርርብና ታማኝነት ከያሉበት በጥቅሻ እየተጠራሩ የተመደቡ በመሆናቸው ለአመራርነት ተሹመው የተረከቡበትን ቢሮ መደበኛ አገልግሎት ተርም (tenure of their office) በብቃት አጠናቅቀው ያስረከቡት ስለመኖራቸው አጠራጠራለሁ፡፡ ልክ እንደሁኖቹ ሁሉ ብዙዎቹ መሀል ላይ ክስ ቀርቦባቸው ወንበራቸውን ተነጥቀው ለመውጣት ተገድደዋል፡፡

ዕድሜ ለእነሱ አሁን ላይ ዩኒቨርሲቲው በመዘጋትና አለመዘጋት መሀል እየተንገዳገደ ይገኛል፡፡ ከአዲሱ የትምህርት ጥራት አገር-አቀፍ የትምህርት ሚንስቴር የትኩረት አቅጣጫ ጋር በተያያዘ አሁን ካሉን ዩኒቨርሲቲዎች የተወሰኑት በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት ሙሉ በሙሉ ባይዘጉ እኳን ከደረጃቸው ዝቅ ብለው በጁኒየር ተቋሚነት ለመቀጠል እንደሚገደዱ አሁን እየተስተዋለ ያለው ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚገቡ ተማሪዎች ቁጥር እጅግ ከፍተኛ በሆነ ሁኔታ መቀነሱ፤ ተማሪዎች ወደ ተቋሞቹ በምርጫቸው ሊመጡ ያለ መሆኑና መሰል ተጨባጭ ሀቆች ከበቂ በላይ ያስረዱናል፡፡

በዚህ መሰረት አሁን ካሉት ተቋማት ውስጥ ሳይዘጉ መትረፍ የሚችሉት ዩኒቨርሲቲዎች ከፍተኛ የሆነ የአመራር ብቃት፤ አርቆ-አስተዋይነትና ተቋማዊና ማህበረሰባዊ ተቋርቋሪነት የተላበሰ ማነጅመት ጥረት ከታከለላቸው ብቻ እንደሚሆን መረዳት ያስፈልጋል፡፡

በዚህ ረገድ ስለ ዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የበላይ አመራር ሽግግር ዕጣ-ፈንታ ለማህበረሰቡ እሳካሁን ድረስ በግልፅ የተነገረ ነገር ቢኖር የየኒቨርሲቲው የበላይ አመራር ብልሹ የፋይናንስ አያያዝና ምዝበራው በኦዲት ሪፖርት መረጋገጡ ሲሆን እነዚህ በሌብነትና ምዝበራ የተሳተፉት ግለሰቦች ከሀላፊነት ስለመታገዳቸው እንኳን ምንም በይፋና በኦፊሴል የተገለፀ ነገር የለም፡፡

ሌላው እኩል አሳሳቢ የሚሆነው እነዚህ ግለሰቦች ሲነሱ የሚተኳቸው ሰዎች የሚሰየሙት በምን መንገድ ነው የሚለው ጥያቄ ይሆናል፡፡ ሌባ በአዲስ ሌባ፤ መዝባሪ በሌላ መዝባሪ ብቃት-አልባ ማነጅመንት በሌላ ልፍስፍስ እና ለህብረተሰቡና ተቋሙ ራዕም ሆነ ተቋርቋሪነት በሌለው ሌላ ደንታ-ቢስ መንገደኛ በተለመደው የካድሬ ጥቅሻ ከሩቅ ተጠራርተው እንደ አንድ ተራ የወረዳ አስተዳዳሪ እንዳይመደቡ የተቋሙ ማህበረሰብ በንቃት መከታተልና መታገል ይኖርበታል፡፡

በምዝበራ የተዘፈቀው አመራር እንዲነሳ ከመታገል ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ የበለጠ ወሳኝ እርምጃ ግን አዲስ ማነጅመንት መተካት ያለበት ግልፅ የሆነ የሀላፊነት ቦታዎች (positions) የሚመጥን መስፌርት ወጥቶላቸው እና ይህም በማስታወቂያ በብዙሐን መገኛኛ በግልፅ ይፋ ተደርጎ መስፌርቱን የሚያሟሉት ተወዳድረው ቦታን አሸናፊው ተለይቶ ሲረከበው ብቻ ነው፡፡

አዲሶቹ ሀላፊዎች በዚህ መንገድ መሰየማቸውን በማረጋገጥ ረገድ የተቋሙ ማህበረሰብ ሙሉ መብት ያላቸው እንደመሆኑ ሁሉ መብታቸውን ተጠቅመው በሹመት ሂደቱ ተፅዕኖ መፍጠር ከቻሉ አዲሶቹ ሀላፊዎች ወደፊት የማህበረሰቡን የልብ ትሪታ እያዳመጡ ለማስተዳደር የሚገደዱ ሲሆን ነገር ግን ማህበረሰቡ በፖለቲካ ካድሬዎች ከየትም ተጠርተው የተመደቡላቸውን በዝምታ የሚቀበሏቸው ከሆነ ግን ተሹዋሚዎቹ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ ታማኝነታቸውን ለማህበረሰቡ ሳይሆን አምጥተው ለሾሙዋቸው ካድሬዎች ስለሚሆን ምዝበራውም ሆነ ብልሹ አሰራር እየተንገዳገደ ያለው ዩኒቨርሲቲው እስከሚዘጋ ድረስ ይቀጥላል፡፡

በየማህበራዊ ሚዲያ እንደሚናፈሰው ከሆነ የዩኒቨርሲቲው አዲስ አመራር ግልፅነት በሌለው መንገድ በካድሬዎች ምደባ እየሔደ መሆኑ ይሰማል፡፡ በእሰከ ዛሬው ሂደት በየዘመኑ ስልጣን ላይ የነበሩት የደኢህዴን ካድሬዎች ይቀርበኛል ያሏቸው ግለሰቦች በጥቅሻ ጠራርተው በመመደብ ሲዘርፉትና ሲያስዘርፉት ዩኒቨርሲቲው ሊዘጋ ዳር ላይ እየተንገራገጨ ይገኛል፡፡

የብልፅግና ካድሬች ተመሳሳይ ስሁት ፖለቲካዊ መንገድ በመከተል ተቋሙን በዚህ ቀውጢ ወቅት እንዳያዘጉባችሁ የተቋሙ ማህበረሰብና ጠቅላላው የዎላይታ ህዝብ ነቅታችሁ የመታገል ሀላፊነት ይጠብቃቸዋል፡፡ ግልፅ ያልሆነ ሂደት የሚያስገኘው አንዳችም ግልፅና አዎንታዊ ውጤት ሊኖር አይችልም፡፡

በዶ/ር መድህን ማርጮ የተሰነደ👆

እንደሚታወቀው በሙስናና በብልሹ አሰራር ምክንያት በተነሱ የዎላይታ ሶዶ ዩንቨርስቲ ፕረዚዳንትና ምክትል ፕረዚዳንቶች ከኃላፊነት ተወግደው በትምህርት ምንስቴር በኩል አድስ አመራሮችን በብቃታቸው አስፈትኖና አወዳድሮ ሳይሆን ከተለያዩ ዩንቨርስቲዎች በምደባ ኃላፊነት ቦታ እንደሰጣቸው የዎላይታ ታይምስ ሚዲያ አንድ ከፍተኛ ባለስልጣን ጠቅሶ በዛሬው ዕለት በሰበር መረጃ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።

በዚህም የቀድሞ ምክትል ፕረዝዳንት ዶ/ር ተክሌ ሌዛ ስቀር ሌሎች ሁሉም ከኃላፊነታቸው የተወገዱ ሲሆን አዲሱ ፕረዚዳንት (የጎፋ ተወላጅ) እና አካዳሚክ ፕረዚዳንት ከአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ፤ የምርምር ም/ፕረዚዳንት ከዎላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ መሆኑንም ጭምር አረጋግጠን መዘገባችንም ይታወሳል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

%d bloggers like this: