

በዎላይታ ከ2.4 ቢሊዮን ብር በላይ ለመገንባት በተጀመረው ወይቦ መስኖ ፕሮጀክት ምክንያት የካሣ ገንዘብ ከተከፈላቸው 20 ግለሰቦች መካከል አምስቱ የአመራር ቤተሰብና ግድቡ ከሚሠራበት ቀበሌ ውጭ የመጡ ስለመሆኑ ተረጋገጠ።
ከፌደራል እስከ ቀበሌ ደረጃ የተዘረጋው የሙስና ቅሌት ምክንያት ህብረተሰቡ ከፍተኛ ተስፋ የጣለበት ፕሮጀክት መቆሙ ስጋት መፍጠሩም ተነግሯል።



እስካሁን በተደረገው ማጣራት በቦሎሶ ሶሬ ወረዳ በኩል የካሣ ክፍያ ከተሠራላቸው ከ401 አባወራዎች መካከል 76 የሚሆኑት በቀበሌው ውስጥ ምንም ይዞታ ያልነበራቸው፣ ከሌላ ቀበሌ የተመዘገቡ የአመራር ዘመዶች፣ በመንግስት የወል መሬት ያስመዘገቡ፣ ደላሎች፣ ወዘተ መሆናቸውን በዎላይታ ዞን የተቋቋመ አጣሪ ኮሚቴ ማረጋገጡን አንድ የኮሚቴው አባል ለዎላይታ ታይምስ ሚዲያ ቢያረጋግጥም እስካሁን ማስተካከያ እርምጃ አለመወሰዱ ተገልጿል።
በቦሎሶ ቦምቤ ወረዳ የመስኖ ፕሮጀክት ተደራሽ በሚሆንበትና የመስኖ ካናል በሚሠራበት አከባቢዎች በተደረገው ማጣራት 56 ሕገወጥ መሆናቸውን አብራርተዋል።
በሁለቱም ወረዳዎች የካሣ ግምት ሲሠራ ከአመራሮችና ደላሎች ጋር በመመሳጠር ከፍተኛ የዋጋ ግነት (እስከ 1000%) የተመዘገበም እንዳለ መረጃዎች ያመላክታሉ።
ለአብነት፦ 2 በቆርቆሮ የተሠሩ መጋዘኖችና አንድ ዝቅተኛ የቡና መፈልፈያ ማሽን ለተከለው ግለሰብ 28.7 ሚሊዮን ብር እንዲከፈልለት ተደርጓል፤ ለአንዲት ጎልማሳ እማወራ 14 ሚሊዮን ብር ተከፍሎላታል።
በዚህ የካሣ ገንዘብ ዝርፊያ ውስጥ የቀድሞ የቦሎሶ ሶሬ ወረዳ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት፣ የቀድሞ የቦሎሶ ቦምቤ ወረዳ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት፣ ከዎላይታ ዞንና ከደቡብ ክልል፣ ከፌደራል የተወሰኑ ከፍተኛ አመራሮች እንደተሳተፉበት ለዎላይታ ታይምስ ሚዲያ የደረሰው መረጃ ያረጋግጣል።
የፌዴራል መስኖና ቆላማ አከባቢዎች ሚኒስቴር የካሣ ገንዘብ እጅግ የተጋነነና በፊት ከተገመተው 600 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ገንዘብ በመጠየቁ እስካሁን ድረስ የንብረት ካሣ በአግባቡ ያልተከፈላቸው 401 አባወራዎች ለከፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ የተዳረጉ ሲሆን የፕሮጀክቱ ግንባታም እንዲስተጓጎል ተደርጓል።
የወይቦ መስኖ ልማት ፕሮጀክት በዎላይታ ዞን በወይቦ ወንዝ ላይ በ2.44 ቢሊዮን ብር በጀት ሕዳር 2014 ዓ/ም የተጀመረ ሲሆን ሲጠናቀቅ 3,429 ሄክታር መሬት የማልማት አቅም አለው ቢባልም በአሁኑ ወቅት ካሳ ባይከፈልም ለልማት ሲባል ነዋሪዎች አርሶ ከሚበሉበት መሬት ለቆ ሌላ ቦታ ቢሄዱም የግንባታ ሂደት መቆሙ በአከባቢው ነዋሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ስጋት መፈጠሩን ገልጿል፡፡


ፕሮጀክቱ እስከ መጋቢት ወር 2015 ዓ/ም መጨረሻ ድረስ አጠቃላይ አፈፃፀሙ 11.3 % ብቻ የደረሰ ሲሆን በሁለት ሎቶች ተከፍሎ የሚገነባ ሲሆን ሎት-1 (የግድብና ተያያዥ ሥራዎች ግንባታ) በደቡብ ውሃ ሥራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅት እንዲሁም ሎት-2 (የመስኖ መሬት ዝግጅት ግንባታ) የሚገነባው ክሮስ ላንድ ኮንስትራክሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ከኦሮሚያ ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን ጋር በጆይንት ቬንቸር በመቀናጀት ሲሆን የፕሮጀክቱ ተቆጣጣሪ መኃንዲስ የደቡብ ዲዛይንና ቁጥጥር ኢንተርፕራይዝ መሆኑን የዎላይታ ታይምስ ሚዲያ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።